05/08/2022
የመረጃ መዛባትን ሰዎች እንዲከላከሉ የሚያነቃቃ የንግግር መድረክ ተካሄደ፡፡
የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ ተሳትፎና ኢንተርፕራይዝ ልማት ምክትል ፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ከሕግ ኮሌጅ ጋር በመተባበር በማህበራዊ ሚዲያ አጠቃቀምና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የሚስተዋለውን ችግር ለመከላከልና ግጭቶችን ለመቀነስ የሚያስችል መድረክ ነው የተዘጋጀው፡፡
ሐምሌ 28/2014 ዓ.ም በአፍረን ቀሎ አዳራሽ በተዘጋጀው መድረክ ላይ የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ ተሳትፎና ኢንተርፕራይዝ ልማት ምክትል ፕሬዝዳንት ዶ/ር ይስሀቅ ዩሱፍ ባደረጉት ንግግር ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከቀበሌ አንስቶ እስከ አገር አቀፍ ደረጃ በፖለቲካ ልዩነት፣ በብሔርና በሃይማኖት አክራሪነት እንዲሁም በድንበርና በሌሎች ሀብቶች ምክንያት ግጭቶች እንዲቀሰቀሱና እንዲባባሱ ማህበራዊ ሚዲያ ትልቅ ድርሻ እንደነበረው ጠቁመው በማህበራዊ ሚዲያና ተያያዥ ጉዳዮች ሳቢያ የሚስተዋለውን ችግር ለመከላከል እንዲቻል መድረኩ መዘጋጀቱን ጠቁመዋል።
ዶ/ር ይስሀቅ አክለውም እንደተናገሩት በአሁኑ ጊዜ በሰዎች መካከል የፖለቲካ ልዩነት፣ የብሔርና የሃይማኖት ልዩነቶች የግጭት መንስኤዎች ሊሆኑ የቻሉት የጥላቻ ንግግሮች በማህበራዊ ሚዲያዎች ላይ በመስፋፋታቸውና ህብረተሰቡ እውነታውን ከማጣራት ይልቅ በቀላሉ እየተቀበለ በመሆኑ ግጭቶች እንዲከሰቱ ፣ የብዙ ወገኖቻችን ህይወት እንዲጠፋና ሰዎች ከቀዬአቸው እንዲፈናቀሉ ምክንያት ሆኗል።
ባለፉት ሶስት ወራት ይህንን ችግር ለማስቀረት እንዲቻል ከዩ ኤስ ኤይድ ጋር በመተባበር በኦሮሚያ ክልል በምስራቅና ምዕራብ ሐረርጌ ዞኖች ፣ በሐረሪ ክልልና ድሬደዋ መስተዳደር የተለያዩ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረኮችን ለሀይማኖት አባቶች ፣ ለመንግስት ኮሙዩኒኬሽንና የሥራ ኃላፊዎች ፣ ተማሪዎችና ለዩኒቨርሲቲ ሠራተኞች መስጠቱን አስረድተዋል፡፡
በመድረኩ ላይ አቶ ብርሀኑ ራቦ 'የህይወት ሂደት መልሶ ግንባታ' በሚል ርዕስ እንዲሁም ወጣት መሐመድ አሊ ዩሱፍ (ቡርሀን አዲስ) 'በጥልቅ ማሰብና መረጃን መመዘን' በሚል ርዕስ አነቃቂ ንግግር ያደረጉ ሲሆን የጥላቻ ንግግርን ማረቅ እንደሚያስፈልግና ሁሉንም መረጃ ሳያጣሩ እንዳለ መቀበል በህይወታችን ውስጥ ሀሳቦቻችንና በየቀኑ የምንወስዳቸው እርምጃዎቻችንን ስለሚያስቱ እንደ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ የተሳሳቱ መረጃዎችንና የጥላቻ ንግግሮችን ለመከላከል ለሚያስቻል የነቃ አእምሮ ሊኖረን ይገባል ብለዋል፡፡
የሐረማያ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ምክትል ፕሬዝዳንት ፕሮፌሰር መንግሥቱ ኡርጌ በበኩላቸው ማህበራዊ ሚዲያ ከእያንዳንዳችን ቤት ውስጥ ካሉት ህፃናት አንስቶ እሰከ በተማሩ ሰዎች ላይ ሁሉ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ እያደረሰ መሆኑን ጠቁመዋል።
በአሁኑ ጊዜ ሀሰተኛ መረጃዎች እንዲሁም የጥላቻ ንግግሮች በአገራችን ብቻ ሳይሆን በመላው ዓለም ላይ ከፍተኛ ችግር በመፍጠር ላይ እንደሚገኙ ፕሮፌሰር መንግስቱ ጠቅሰው የሀሰተኛ መረጃዎችንና የጥላቻ ንግግሮችን ለመቀነስ መሰል መድረኮች ማዘጋጀት ጠቀሜታው ከፍተኛ በመሆኑ ከመድረኩ ያገኘነውን እውቀት ወደተግባር በመቀየር ራሳችንን ለውጠን ለሌሎች መትረፍ ይጠበቅብናል ብለዋል፡፡
የሕዝብና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት
ዘጋቢ ፡ ሸምሸዲን መሀመድ
ፍቶግራፍ ፡ ፎአድ አህመድ አሊ
ሐምሌ28/ 2014 ዓ.ም