19/08/2022
የትግራይ ህዝብ የህወሃት እስረኛ ሆኖ ሊቀጥል አይግባም ሲሉ ቢልለኔ ስዩም ተናገሩ
የሰላም አማራጭ አብይ ኮሚቴ ለሰሜኑ ግጭት ሰላማዊ እልባት ለመስጠት ያፀደቀው የሰላም ምክረ ሃሳብ መንግስት ለሰላማዊ አማራጭ ያለውን ቁርጠኝነት ያረጋገጠ መሆኑን የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ፕሬስ ሴክሬታርያት ኃላፊ ቢልለኔ ስዩም ገልጸዋል።ኃላፊዋ ለአለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ስለ ሀገሪቱ ወቅታዊ ሁኔታ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል ለተከሰተው ግጭት ሰላማዊ መፍትሄ በመስጠቱ ዙሪያ፥ በመጪዎቹ ሳምንታት የተኩስ አቁም እንዲደረስ፣ የሰላም ውይይት እንዲሁም ሌሎች በእንጥልጥል የቀሩ ጉዳዮች ደግሞ በብሄራዊ ምክክሩ እንዲዳሰሱ ለማድረግ የሚያስችል የሰላም ረቂቅ ሰነድ ይፋ መደረጉን አንስተዋል፡፡
የሰላም ውይይት ምንም አይነት ቅድመ ሁኔታ የሚያስፈልገው አይደለም ያሉት ቢልለኔ፥ የትግራይ ህዝብ የህወሃት እስረኛ ሆኖ ሊቀጥል አይግባም ብለዋል፡፡ህወሃት በህገወጥ መንገድ የሰበሰበውን የውጭ ምንዛሪ፣ ለመጠባበቂያነት የተቀመጡ የነዳጅ፣ የምግብና የመሳሰሉ ግብአቶችን ለዚሁ እኩይ ተልዕኮው እንደሚጠቀም ጠቁመዋል።ቡድኑ ይህን ሁሉ እኩይ ተግባራት እየፈፀመ ባለበት ሁኔታ መንግስት ለሰላም ቅድሚያ በመስጠት ነገሮችን በሆደ ሲፊነት ሲመለከት መቆየቱን ተናግረዋል፡፡
መንግስትየሰላም ጥረቶችን ሲያደርግ እንደቆየና በህወሃት በኩል ለሰላም አማራጭ የተሰጠ ሥፍራ አለመኖሩን ገልጸዋል።ህወሃት የሀሰት ክሶችን በማንሳትና የተሳሳቱ ትርክቶችን በመንዛት ዓለም አቀፉን ማህበረሰብ በተሳሳተ አቅጣጫ ለመምራት ሙከራ እያደረገ እንደሚገኝ አመላክተዋል፡፡ በትግራይ ክልል ዙሪያ ብዥታ ሊኖር እንደማይገባና በክልሉ መልሶ ግንባታና መሰረታዊ ድጋፎች ላይ መንግስት እየሰራ እንደሚገኝ ጠቅሰዋል፡፡