21/08/2026
የማይንቀሳቀስ ንብረት (ቤትና መሬት) ሲገዙ ማረጋገጥ ያለብዎት 5 ወሳኝ ነገሮች” ፡ የሕይወት ዘመን ጥረትዎ በአጭበርባሪዎች እንዳይበላ!
የዓመታት ልፋትና ጥረትዎን አውጥተው የመሬት ወይም የቤት ግዢ ከመፈፀምዎ በፊት “የባለቤትነት ማረጋገጫ ደብተር (ካርታ)” ማየት ብቻ በቂ ይመስልዎታል? በፍፁም አይደለም! ይህንን ስህተት ከሠሩ ገንዘብዎንም መሬቱንም ሊያጡ ይችላሉ።
በአገራችን የመሬትና የቤት ሽያጭ ከፍተኛ የገንዘብ ዝውውር የሚደረግበት ቢሆንም፤ በዚያው ልክ በርካታ ዜጎች የሚታለሉበትና የሕይወት ዘመን ቁጠባቸውን የሚያጡበት ዋናኛ መስክ ሆኗል። ብዙ ጊዜ ገዢዎች በደላላ ግፊት ወይም “ካርታ አለው” በሚል መተማመን ብቻ ውል ውስጥ ይገባሉ።
ነገር ግን መሬት በኢትዮጵያ ሕገ-መንግሥት አንቀጽ 40(3) መሠረት የሕዝብና የመንግሥት ንብረት በመሆኑ፤ እኛ የምንገዛውና የምንሸጠው “የመጠቀም መብትን” (Leasehold/Possession) ብቻ ነው።
ስለሆነም ግዢ ከመፈፀምዎ በፊት የሚከተሉትን 5 ነጥቦች በሕግ ፊት ማረጋገጥ አለብዎት፡
1. የካርታው ትክክለኛነት (Search)፦ ካርታው በእጅዎ ቢኖርም፤ በክፍለ ከተማ ወይም በወረዳ የመሬት ማኔጅመንት ቢሮ በአካል ቀርበው መሬቱ ዕገዳ (Injunction) ያለበት መሆን አለመሆኑን እና ካርታው በሲስተም ውስጥ መኖሩን ማረጋገጥ አለብዎት።
2. የጋራ ንብረትነት (የባልና ሚስት)፦ መሬቱ በባል ወይም በሚስት ስም ብቻ የተመዘገበ ቢሆንም፤ በጋብቻ ጊዜ የተፈራ ከሆነ የሁለቱም የጋራ ንብረት ነው። የትዳር አጋር ሳይስማማና ሳይፈርም የሚደረግ ሽያጭ በሕግ ፊት ፈራሽ (Void) ይሆናል።
3. ክስ ወይም የፍርድ ቤት ዕገዳ፦ መሬቱ ወይም ቤቱ በፍርድ ቤት ክስ ሂደት ላይ ያለ ወይም በዕዳ ምክንያት በባንክ የተያዘ (Mortgage) መሆን አለመሆኑን ማረጋገጥ።
4. የመንግሥት ልማት (የማስተር ፕላን) ስጋት፦ ቦታው ወደፊት ለመንገድ ማለፊያ፣ ለፓርክ ወይም ሌላ የመንግሥት ልማት የተያዘ (አረንጓዴ ቦታ) መሆን አለመሆኑን ከወረዳው ማስተር ፕላን ማረጋገጥ።
5. ሕጋዊ ውል ማረጋገጫ፦ በኢትዮጵያ የፍትሐ ብሔር ሕግ ቁጥር 1723 እና 2877 ላይ በግልጽ እንደተደነገገው፤ ከማይንቀሳቀስ ንብረት (ከቤትና መሬት) ጋር የተያያዙ ማንኛውም ውሎች በሕግ ፊት የጸኑ እንዲሆኑ በግልጽ በጽሑፍ መደረግና በሕግ ሥልጣን በተሰጠው አካል (በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ ኤጀንሲ/ውልና ማስረጃ) ፊት ቀርበው መመዝገብ አለባቸው። የመንደር ውል ወይም በደላላ ፊት የሚደረግ ውል በሕግ ፊት ዋጋ የለውም። ይህንን የሕግ ድንጋጌ የበለጠ ያጠናከረውና በሙሉው አገሪቱ ያሉ ፍርድ ቤቶች ላይ አስገዳጅ ሕጋዊ ትርጉም የሰጠው የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ሰበር ሰሚ ችሎት (በመዝገብ ቁጥር 21448 እና መሰል መዝገቦች) ላይ የሰጠው ውሳኔ ነው።
የሰበር ችሎት ውሳኔው እንደሚያስረዳው፦
“በማይንቀሳቀስ ንብረት ላይ የሚደረግ የሽያጭ ውል በሕግ ሥልጣን በተሰጠው የመንግሥት አካል ፊት ቀርቦ ካልተመዘገበ፤ ውሉ እንደ አልተደረገ (Void) ይቆጠራል። ውሉ ሕጋዊ ውጤት ስለማይኖረውም ገዢው የባለቤትነት መብት እንዲተላለፍለት የመጠየቅ መብት የለውም።
ሰዎች በተደጋጋሚ የሚሠሩት ስህተት፦ "ሰነዱ ዋናው ነው" በሚል በመተማመን ብቻ፤ የመሬት አስተዳደር ቢሮ ሄደው ሳይንቀሳቀሱና ሳይመረምሩ ሙሉ ገንዘብ መክፈል።
አጭበርባሪዎች ከአንድ በላይ "የመጠባበቂያ" ወይም የሐሰት ካርታ አዘጋጅተው በአንድ ጊዜ ለ3 እና 4 ሰው ሊሸጡ እንደሚችሉ አይዘንጉ። በተጨማሪም "ሻጭ የዋህ ሰው ነው፤ ምስክሮችም አሉኝ፤ ደረሰኝም ተጻጽፈናል" በሚል መተማመን የውልና ማስረጃ ምዝገባን ማዘገየት ወይም መተው። ሻጭ ከዓመታት በኋላ ዋጋ ሲጨምር ሃሳቡን ቀይሮ "ውሉ በሕግ ፊት አይጸናም፤ መሬቴን/ቤቴን መልሱልኝ" ብሎ ፍርድ ቤት ቢከሰዎት፤ ቤቱ ላይ መብት እና ጥቅም አለኝ የሚል 3ኛ ወገን ተከራክሮ ቢክስ ሰበር ችሎት በሰጠው አስገዳጅ ትርጉም መሠረት ንብረቱን ለሻጭ እንዲመልሱ ይገደዳሉ።
እርስዎ የሚመለስልዎት የከፈሉት ዋና ገንዘብ ብቻ ሊሆን ይችላል፤ ይህም በዋጋ ንረት ምክንያት የዛሬውን ዋጋ አይተካም።
ተግባራዊ የሕግ ምክር፦ ማንኛውንም የቅድመ-ክፍያ (Advance/Advance Payment) ከመክፈልዎ በፊት ከሻጭ ጋር በመሆን ወደ መሬት አስተዳደር ቢሮ በመሄድ የንብረቱን ነፃነት ማረጋገጫ (Clearance) በጽሑፍ ይጠይቁ።
ውል ከመፈፀምዎ በፊት የሕግ ባለሙያ ወይም ጠበቃ ማማከር የሚጠይቀውን አነስተኛ ክፍያ በመፍራት፤ የነገውን ትልቅ ክሳራ አይጋብዙ።